ታህሳስ 13 ቀን 2014 (ቱሚ) መንግስት አንድ ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንና የኢትዮጵያ ወዳጆችን ለመቀበል የሚያደርገውን ዝግጅት ማጠናቀቁን ገለጸ።
ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ በውጭ አገር የሚኖሩ አንድ ሚሊዮን ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን እስከ ታህሳስ 29 ቀን 2014 ዓ.ም ወደ አገር ቤት እንዲመጡ ጥሪ ማድረጋቸው ይታወቃል።
የአገር ቤት ጥሪውን የሚያስተባባር ብሔራዊ ኮሚቴ ተዋቅሮ ወደ ስራ መግባቱ የሚታወቅ ሲሆን፤ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርና የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር ደመቀ መኮንን የሚመራው ኮሚቴ በዝግጅቱ ዙሪያ ዛሬ ውይይት አድርጓል።
ኮሚቴው ዳያስፖራው ወደ አገር ቤት በሚመጣበት ወቅት ከቪዛ አሰጣጥ፣ ትራንስፖርት፣ የእንግዶች ማረፊያና ሌሎች አገልግሎት መስጫዎች ጋር በተያያዘ ምቹ መስተንግዶ እንዲያገኝ ከማድረግ አኳያ እየተከናወኑ ባሉ ስራዎች ላይ መምከሩን የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ገልጿል።
ወደ አገር ቤት የሚመጡ ዳያስፖራዎች በአገር መልሶ ግንባታ ሂደትና የውጭ ሃይሎችን ያልተጋባ ጫና በመቃወም በሚካሄዱ ሰላማዊ ሰልፎች ላይ የሚሳተፉባቸው የተለያዩ መርሃ ግብሮች መዘጋጀታቸውን አመልክቷል።
የኢትዮጵያ አየር መንገድ፣ ኢትዮ ቴሌኮም፣ የመንግስትና የግል ሆቴሎችና ሌሎች አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ወደ አገር ቤት ለሚመጡ ዳያስፖራዎች የዋጋ ቅናሽ እንደሚያደርጉ ማሳወቃቸው ተወስቷል።